አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 4/2013 ዓ.ም. አዳዲስ የብር ኖቶችን በማሠራጨትና የቀድሞዎቹን ኖቶች በመቀየር ሂደት ወደ ባንኮች የሚሰበሰበው ገንዘብ መጨመሩን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አስታወቀ።
ትናንት በባንኩ አዳራሽ በተካሄደው የፕሬስ መግለጫ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ምክትል ገዥ አቶ ሰሎሞን ደስታ እንደገለጹት በገንዘብ ቅያሬው ሂደት አዳዲስ በተከፈቱ አካውንቶች ከ13 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ መሰብሰብ ተችሏል።
በገንዘብ ቅያሬው ሂደት እጅግ በርካታ አዳዲስ አካውንቶች መከፈታቸውን ያመለከቱት ምክትል ገዥው፣ ይህም ገንዘብን ወደ ባንክ እንዲሰበሰብ የማድረግን ዕቅድ ለማሳካት የሚያስችል መሆኑንም አመልክተዋል።
እስካሁን ብር 90 ነጥብ 4 ቢሊዮን አዲስ የብር ኖቶች ለባንኮች መሠራጨታቸውን አቶ ሰሎሞን አመልክተዋል።
አሮጌውን የብር ኖት በመተለከተ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እስካሁን ከባንኮች የሰበሰበው ገንዘብ 74 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር መድረሱንም አስረድተዋል።
የብር ኖቶቹን የመቀየር ሂደት ተጠናክሮ መቀጠሉንና በሁሉም ባንኮች ሁሉም ቅርንጫፎች አገልግሎቱ እየተሠጠ መሆኑን ያመለከቱት አቶ ሰሎሞን፣ ሕብረተሰቡም ሳይዘናጋ በቀሪዎቹ ቀናት ወደ ባንክ ቅርንጫፎች በመሄድ አሮጌውን የብር ኖት እንዲቀይር አሳስበዋል።
የብር ለውጡንም በተመለከተ ቀደም ብሎ ይሠራበት እንደነበረው እስከ ብር 5ሺህ በጥሬ ገንዘብ እና ከብር 5ሺህ በላይ ከሆነ ደግሞ ሂሳብ በመክፈት መለወጥ እንደሚቻል አስታውቀዋል።
በባንኩ የከረንሲ ማኔጅመንት ዳይሬክተር አቶ አበበ ሰንበቴ በበኩላቸው፣ ስለ አዳዲሱ የብር ኖቶች ምስል፣ አስመስሎ ከተሠራው ብር በቀላሉ ስለሚለዩባቸው ገጽታዎች፣ ስለብር አያያዝና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ ሠጥተዋል።