Category: Uncategorized
NBE PRESS RELEASE
NBE PRESS RELEASE
ማሻሻያ የተደረገበትን የወርቅ ዋጋ ስለማሳወቅ
የባንኩ ሴት ሠራተኞች ዓለምአቀፍ የሴቶች ቀንን አከበሩ
የባንኩ ሴት ሠራተኞች ዓለምአቀፍ የሴቶች ቀንን አከበሩ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሴት ሠራተኞች የዘንድሮውን የዓለም የሴቶች ቀን በድምቀት አከበሩ። ቀኑ “እኔም የእህቴ ጠባቂ ነኝ” በሚል መሪ ቃል በአገርአቀፍ ደረጃ ለ47ኛ ጊዜ ተከብሮ ውሏል።
የካቲት 29 ቀን 2015 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ በባንኩ አዳራሽ የተከናወነውን ሥነሥርዓት በንግግር የከፈቱት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የኮርፖሬት ሰርቪስ ም/ገዥ አቶ እዮብ ገብረኢየሱስ ዕለቱ ተከብሮ የሚውለው ለሴቶች የማይመቹ ሁኔታዎችን ማስወገድና በተለያየ መልክ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን መታገል እንደሚገባ ለማስገንዘብ መሆኑን ገልጸዋል።
በርግጥም “እኔም የእህቴ ጠባቂ ነኝ” በሚለው መሪ መልዕክት መሠረት ሁላችንም ጭቆናና ጥቃቶችን ልንታገላቸው ይገባል ብለዋል።
በተቋም ደረጃ ለሴቶች ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠር፣ አቅማቸውን ማሳደግና ወደ ሥልጣን ማምጣት የባንኩ አመራር የሚረዳው ጉዳይ ነው ያሉት ም/ገዢው፣ ሴቶችም በበኩላቸው ለዚህ አስተዋፅኦ ማድረግና ዝግጁ ሆኖ መገኘት እንደሚኖርባቸው አመልክተዋል።
የባንኩ የሴቶችና ወጣቶች ጉዳይ ቺፍ ኦፊሰር የሆኑት ወይዘሮ አምባወርቅ መኮንን ዕለቱን አስመልክቶ በሠጡት ገለጻ የሴቶችን ጉዳይ በሁለንተናዊ መልኩ ለመድረስ የማያቋርጥ ትግል እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል።
ዕለቱ በአገራችን ለ47ኛ፣ በዓለምአቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ112ኛ ጊዜ ቢከበርም፣ አሁንም በሴቶች ላይ የሚደርሰው ጥቃት አልቀረም፤ ሴቶችን ማጎናጸፍ የሚገባው ድል ገና በሚገባ ማሳካት አልተቻለም ብለዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ዕለቱን አስመልክቶ ቀደም ካሉት ዓመታት ጀምሮ ያደካሄዳቸውን መርሐግብሮች ያስታወሱት ወይዘሮ አምባወርቅ፣ በተጓዳኝም የባንኩን ሴት ሠራተኞች ከቁጥር፣ ከትምህርት ዝግጅትና አመራር ላይ ካላቸው ተሳትፎ አኳያ በአሀዝ በተደገፈ መረጃ ማብራሪያ ሠጥተዋል።
በመርሐግብሩ መሠረት ከባንኮች ክሊኒክ የመጡ ዶክተሮች በማህጸን ጫፍ ካንሰርና በጡት ካንሰር ላይ ትምህርታዊ ገለጻ የሠጡ ሲሆን፣ ከኦፕሪፍስ መጠለያ ማዕከል በመጡ ሕጻናት ኪናዊ ዝግጅት ቀርቧል፤ የዳቦ ቆረሳና ቡና የማፍላት ሥነሥርዓትም ተካሂዷል።
የኦፕሪፍስ ማዕከል ሀላፊ ወይዘሮ እንግዳወርቅ ታደሰ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ቀደም ሲል በህዳር 2015 ዓ.ም በማዕከሉ ተገኝቶ ያደረገውን ጉብኝትና ድጋፍ አስታውሰው፣ በቀጣይም ባንኩ ለማዕከሉ የሚያደርገው ድጋፍ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
ሁሉም ወላጅ ልጆቹን (ሴቶችንም ሆነ ወንድ ልጆቹን) በቤትም ሆነ በውጭ፣ እንዲሁም ከቅርብ ዘመድም ጭምር መጠበቅ እንዳለበት ማዕከሉ የሚንከባከባቸው የጥቃት ሰለባ ሕጻናት መልክዕት መሆኑን ወይዘሮ እንግዳወርቅ አሳስበዋል። ምክንያቱም አብዛኞቹ ጥቃቶች ከሩቅ ሳይሆን ከቅርብ በተለይም “የእኔ” ከሚሉት ወገን የሚመጡ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
በመጨረሻም የለውጥ ማኔጅመንት፣ ዕቅድና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አባተ ምትኩ እንዳሉት፣ “እኔም የእህቴ ጠባቂ ነኝ” የሚለውን መሪ ቃል ሁሉም ከልቡ ተግባራዊ ማድረግ አለበት።
በተቋም ደረጃ ሴት ሠራተኞችን በአቅም ግንባታ ከማሳደግና ወደ አመራር ሠጪነት እንዲበቁ ከማድረግ ጎን ለጎን ባንኩን ለሴቶች አመቺ የሥራ ቦታ እንዲሆንላቸው ሁሉንም አስቻይ ነገሮች ተግባራዊ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
የሕጻናት ማቆያ (day care) ማዕከሉን ግንባታና ሙሉ ዝግጅቱን አጠናቅቆ በፍጥነት ሥራ ላይ ማዋል የሚያስፈልግ መሆኑን የጠቀሱት አቶ አባተ፣ ይህም የባንኩ ሴት ሠራተኞች ሥራቸውን በተረጋጋና በውጤታማነት እንዲያከናውኑ ለማስቻል በእጅጉ የሚያግዝ መሆኑን አብራርተዋል።
በተጨማሪም ነፍሰጡር እናቶች በመንግሥት የተሠጣቸው የወሊድ ፈቃድ አጠቃቀም ላይ በራሳቸው በነፍሰጡሮቹ ፍላጎት መሠረት ተመቻችቶ ተግባራዊ ቢደረግ መልካም መሆኑን አቶ አባተ ጠቁመዋል።
በዓመት አንድ ጊዜ በሚከበረው በሴት የሴቶች ቀን ላይ የባንኩ መካከለኛና ከፍተኛ ሴት አመራር አባላት እንደሚጠበቀው አለመሳተፋቸውን እንደክፍተት አንስተውታል። አቶ አባተ በየዓመቱ መጠነኛም ቢሆን ለተለያዩ ግብረሰናይ ድርጅቶች ድጋፍ እየሠጠንና ደማቅ በሆነ ሁኔታ እንድናከብር ለሚፈቅድልን የባንኩን የበላይ አመራር፣ እንዲሁም ጥሪያችንን አክብረው በበዓሉ ላይ ለሚታደሙ ሠራተኞች፣ በማህጸን ጫፍ ካንሰርና በጡት ካንሰር ላይ ትምህርታዊ ገለጻ ለሰጡት ዶክተሮች በመጨረሻም ለኦፕሪፍስ ማዕከል ምሥጋና አቅርበዋል።
የባንኩ ሠራተኞች 127ኛውን የአድዋ ድል በዓል አከበሩ
የባንኩ ሠራተኞች 127ኛውን የአድዋ ድል በዓል አከበሩ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሠራተኞችና የማኔጅመንት አባላት 127ኛውን የአድዋ ድል በዓል በድምቀት አከበሩ።
የካቲት 22 ቀን 2015 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ በባንኩ አዳራሽ በተከናወነው ሥነሥርዓት ላይ የማኔጅመንት አባላትና የባንኩ ሠራተኞች፣ የተገኙ ሲሆን፣ በልዩ ልዩ ሁነቶች መርሐግብሩ ተከናውኗል።
መርሐግብሩን በንግግር የከፈቱት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የኮርፖሬት ሰርቪስ ም/ገዥ አቶ እዮብ ገብረኢየሱስ የአድዋ ድል ለኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካውያን ብሎም ለመላው ጥቁር ሕዝብ የነጻነት ተምሳሌት መሆኑን ገልጸዋል።
የአድዋ ድል ጥቁር ሕዝብም አሸናፊ እንደሆነ ለነጮቹም ሆነ ለመላው ዓለም ትምህርት የሠጠ መሆኑንና ለጸረ-ኮሎኒያሊዝም ትግል መነሻ ሊሆን እንደቻለ ታላላቅ ምሁራንና የአገራት መሪዎች ያረጋገጡት ጉዳይ መሆኑንንም አቶ እዮብ አብነት ጠቅሰው አስረድተዋል።
ም/ገዢው እንዳስረዱት ከኔልሰን ማንዴላ ቀጥሎ የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት በመሆን ያገለገሉት ታቦ ምቤኪ በአንድ ወቅት ባደረጉት ገለጻ የአድዋ ድል ለነጮች የሚያስደነግጥ ትምህርት የሠጠ፤ ለተቀረው የዓለም ሕዝብ የነፃነት ፋና ወጊ መሆን የቻለ ትልቅ የታሪክ ክስተት መሆኑን አስረድተዋል።
“በመሆኑም የዘንድሮውን 127ኛ የአድዋ ድል በዓል ስናከብር አባቶቻችን ምን ያህል አኩሪ ታሪክ ሠርተው ያለፉ መሆኑን የምናስታውስበትና እኛም በአንድነት፣ በጀግንነትና በጽናት ታሪክ መሥራት የሚጠበቅብን መሆኑን ያስረዳል” ሲሉ አቶ እዮብ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
የለውጥ ማኔጅመንት፣ ዕቅድና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አባተ ምትኩ አድዋን በተመለከተ ባቀረቡት አጭር ገለጻ፣ አድዋ በአባቶቻችን ከፍተኛ ተጋድልዎ የተደረገበትና በሚያስደንቅ ጀግንነት ድል የተገኘበት ጦርነት መሆኑን አስረድተዋል።
አቶ አባተ በገለጻቸው ስለ ጠርነቱ መንስዔ፣ ስለጣሊያኖች ዝግጅት፣ በአፄ ምኒልክ ስለተደረገው ጥሪ፣ እቴጌ ጣይቱ ለጣሊያን መንግሥት ስላስተላለፉት መልዕክት፣ ስለሃይል አሰላለፍ በመጨረሻም ስለተካሄደው ጦርነትና አባቶቻችን ስለተጎናጸፉት ድል አብራርተዋል።
በመርሐግብሩ በኢትዮጵያ ሴት ደራሲያን ማህበር አማካኝነት ኪናዊ ዝግጅት የቀረበ ሲሆን፣ የዳቦ ቆረሳ፣ ቡና የማፍላት ሥነሥርዓት መካሄዱ ለዝግጅቱ ድምቀት ሆኗል።
በመርሐግብሩ ማጠናቀቂያ ላይ አድዋን በተመለከተ የጥያቄና መልስ ውድድር የተካሄደ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ም/ገዥና ዋና ኢኮኖሚስት ለተወዳዳሪዎች የተዘጋጀውን ሥጦታ ሸልመዋል።
ም/ገዢው አቶ ፍቃዱ ድጋፌ በመጨረሻ ላይ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያውያን በየትኛውም ጊዜ በአገር ላይ የሚመጡ የውጭ ጥቃቶችን ለመቀልበስ በአንድነት የሚነሱ መሆናቸውን የአድዋ ድል ትክክለኛ ማሳያ መሆኑን አመልክተዋል። በመሆኑም በአድዋ ጦርነት ወቅት በአባቶቻችን ዘንድ የታየውን አንድነት፣ ጀግንነትና ጽናት አሁን ደግሞ እኛ ድህነትን ለማጥፋት በሚደረገው ጥረት ላይ መረባረብ እንዳለብን ምክትል ገዥው አሳስበዋል።
የካፒታል ገበያ ባለሥልጣን የቦርድ አባላት ሥራ ጀመሩ
-
- ይናገር ደሴ (ዶ/ር) የቦርድ ሰብሳቢ ሆነው ተሹመዋል
በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ አህመድ የተሾሙት የካፒታል ገበያ ባለሥልጣን የቦርድ አመራር አባላት ሥራ ጀመሩ።
በቅርቡ ወደ ሥራ እንደሚገባ ይጠበቅ የነበረውን የካፒታል ገበያ ባለሥልጣንን የሚያገለግሉ ስድስት የቦርድ አባላት ኅዳር 22 ቀን 2015 ዓ.ም. መሾማቸው ይታወቃል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ይናገር ደሴ (ዶ/ር) የቦርዱ ሰብሳቢ ሆነው ተሹመዋል።
ሌሎቹ የቦርዱ አባላት የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ወንድምአገኝ ነገራ፣ የካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ብሩክ ታዬ፣ ከተመድ የካፒታል ዴቨሎፕመንት ኢትዮጵያ ጽሕፈት ቤት ደግሞ (ዶ/ር)ኢዮብ ተስፋዬ ፣የሒሳብና የኦዲት ቦርድ ዋና ዳይሬክተሯ ወ/ሮ ሒክመት አብደላ፣ የሴሬብሩስ ፍሮንቲየርስ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ተስፋዬ ኃይለ ሚካኤል እና የአዲስ አበባ ዩነቪርሲቲ መምህር አቶ አባተ አበበ ናቸው፡፡
ከኅዳር 21 ቀን 2015 ዓ.ም. ጀምሮ የባለሥልጣኑ የቦርድ አባል ሆነው እንዲሠሩ የተመደቡት እነዚህ የቦርድ አባላት ማክሰኞ ኅዳር 27 ቀን 2015 የመጀመሪያ ስብሰባቸውን አካሂደው ሥራቸውን ጀምረዋል።
እነዚህ ተሿሚዎች በቦርድ አባልነት የተሰየሙት በካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 1248 /2013 መሠረት ሲሆን፣ በአዋጁ መሠረት የቦርድ አባላቱ የሥራ ዘመን አምስት ዓመት እንደሆነ ተደንግጓል፡፡
በአዋጁ መሠረት የካፒታል ገበያ ማቋቋም ያስፈለገው ካፒታል በማሰባሰብ፣ የገንዘብ ሥርዓቱን በአዲዲስ ፈጠራዎች በመደገፍ እና የኢንቨስትመንት ስጋቶችን የመጋራት አሠራርን በማስፋፋት የአገሪቱን ኢኮኖሚ ልማት ለመደገፍ እንዲቻል ነው። በተጨማሪም በሀገሪቱ የፋይናንስ ሥርዓት ላይ የሚፈጠሩ መዋቅራዊ ስጋቶችን ለመለየት፣ ለመከላከልና ለመቀነስ በካፒታል ገበያ ላይ ጠንካራ የቅርብ ክትትልና የቅኝት ሥርዓት ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት በማስፈለጉ መሆኑን በአዋጁ ተደንግጓል።
የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ሥራ ሊጀምር ነው
የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ሥራ ሊጀምር ነው
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድን (Deposit Insurance) ሥራ ለማስጀመር የሚስችሉ የዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑ ተገለጸ።
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ የሚኒስተሮች ምክር ቤት ባጸደቀው ደንብ ቁጥር 482/2013 መሠረት መቋቋሙን ተከትሎ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ፈንዱን በበላይነት የሚመሩ አምስት የቦርድ አባላትን ሾመዋል።
በዚህም መሠረት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተቋማት ሱፐርቪዥን ምክትል ገዥ አቶ ሰለሞን ደስታ በሰብሳቢነት የተሾሙ ሲሆን፣ የባንክ ሱፐርቪዥን ዳይሬክተር አቶ ፍሬዘር አያሌው፣ አነስተኛ የፋይናንስ ተቋማት ሱፐርቪዥን ዳይሬክተር አቶ መርጋ ዋቅወያ፣ የዘመን ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ ደረጃ ዘበነ፣ እንዲሁም የአነስተኛ የፋይናንስ ተቋማት ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ተሾመ ከበደ የቦርዱ አባል ሆነው እንዲሰሩ የተመደቡ መሆናቸውን ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የተላከው ደብዳቤ አመልክቷል።
የቦርዱ አባል አቶ ፍሬዘር አያሌው ለዜና ኢብባ እንደገለጹት፣ ፈንዱን ሥራ ለማስጀመር እንዲቻል ፖሊሲ ፕሮሲጀርና መዋቅር የማዘጋጀት፣ ሃላፊ የመመደብና ሠራተኞች የማሟላት እንዲሁም የፈንድ ካፒታል የማሰባሰብና ሌሎች ተዛማጅ ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፈንዱ ራሱን ችሎ እስኪደራጅ ድረስ የቢሮ ዕቃዎችን የማሟላትና ሠራተኛ የመቅጠር ሃላፊነቱን እንደሚወጣ አቶ ፍሬዘር ጠቁመዋል።
የፈንዱ አባላት ከሕብረተሰቡ ተቀማጭ ገንዘብ የሚሰበስቡ የፋይናንስ ተቋማት (ባንኮችና አነስተኛ የገንዘብ ተቋማት) መሆናቸውን አቶ ፍሬዘር አመልክተዋል።
የፈንዱ ገንዘብ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በሚከፈት ሂሳብ ውስጥ የሚቀመጥ ሲሆን፣ ሁሉም አባል የፋይናንስ ተቋማት በፈንዱ የሚወሰነውን መነሻ የዓረቦን ክፍያ ወደ ፈንዱ ሂሳብ ገቢ ያደርጋሉ። መንግሥትም መነሻ ካፒታል እንዲሆን ለፈንዱ ሁለት መቶ ሚሊዮን ብር እንደሚመድብ ደንቡ ደንግጓል።
ፈንዱ የተለያዩ የሀብት መሰብሰቢያ መንገዶችን መጠቀም እንደሚችል በደንቡ ውስጥ የተደነገገ ሲሆን፣ የዓረቦን ክፍያዎችን ከአባል የፋይናንስ ተቋማት እንዲሁም የተለያዩ መዋጮዎችን እንደመንግሥትና የልማት አጋሮች ካሉ ሌሎች ምንጮች መሰብሰብና ወደ ራሱ ገቢ ማድረግ እንደሚችል ሥልጣን ተሠጥቶታል።
ፈንዱ ከወደቁ ወይም ከፈረሱ የፋይናንስ ተቋማት ንብረት ማጣራት ከሚገኝ ተመላሽ ገንዘብና በቦርዱ ከሚፀድቁ ሌሎች የፋይናንስ ምንጮች ከሚገኝ ገንዘብ ተጠቃሚ ይሆናል። የፈንዱን ሀብት ገቢ በሚያስገኙለት ዘርፎች ኢንቨስት የማድረግና የማስተዳደር መብት እንዳለውም ተደንግጓል።
ፈንዱን ማቋቋም ያስፈለገው በኢትዮጵያ ቀጣይ የኢኮኖሚ እዴገት የሀገሪቱን የፋይናንስ ሥርዓት ጤናማ፣ ለአደጋ ያልተጋለጠና የተረጋጋ በማድረግ ለማጠናከርና የገንዘብ አስቀማጮች ጥበቃ ለፋይናንስ ሥርዓት ለማረጋጋት በተጨማሪም የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድን እንደ አንድ ተጨማሪ የሀገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ ማረጋጊያ ለማድረግ መሆኑ በደንቡ ተመልክቷል። የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ራሱን የቻለ ሕጋዊ ሰውነት ያለው ተቋም ሲሆን፣ ተጠሪነቱ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ መሆኑን የሚኒስትሮች ምክር ቤት ያወጣው ደንብ ደንግጓል።
Public Notice
Public Notice
Pursuant to the power vested in it under Article 64 (2) of Proclamation No 746/2012 as amended under Proclamation No.1163/2019, the National Bank of Ethiopia is planning to issue a directive on “Risk Based Internal Audit”.
Accordingly, the National Bank of Ethiopia hereby invites any interested/concerned person to comment on the draft directive within one month commencing from the date on which this notice is posted on its website.
Drop your comments at belayt@nbe.gov.et , or send them via the Post Office to Insurance Supervision Directorate at the P.O.Box No. 5550 latest by November 30,2021.